በስዊዘርላንድ የሚኖሩ አንድ ግለሰብ ለሰሊሆም የአዕምሮ ህሙማን መርጃ ማህበር ከ2 ሚሊየን ብር በላይ ድጋፍ አደረጉ
መስከረም 02 ቀን 2015 (ኢዜአ) በስዊዘርላንድ የሚኖሩ አንድ ግለሰብ ከተለያዩ ተቋማትና ግለሰቦች ያሰባሰቡትን ከ2 ሚሊየን ብር በላይ የሚገመት የአይነት ድጋፍ ለሰሊሆም የአዕምሮ ህሙማን መርጃ ማህበር አበረከቱ።
የስዊዘርላንድ አየር መንገድ ሰራተኛ የሆኑት ኤሚ በቀለ ከተለያዩ ግለሰቦችና ድርጅቶች ያሰባሰቧቸውን አልባሳቶችን ጨምሮ ሌሎች ቁሳቁሶችን ነው በዛሬው እለት ያበረከቱት።
እንዲህ አይነት ድጋፎች የሁሉም ሰው ሰብአዊነት መገለጫዎች መሆናቸውን ገልጸው በድጋፉ ትብብር ላደረጉ ሁሉ አመስግነዋል።
በቀጣይም ለማዕከሉ የሚደረጉ ድጋፎችን በማስተባበር የድርሻቸውን አስተዋጽኦ ለማድረግ መዘጋጀታቸውን ተናግረዋል።
የሰሊሆም የአዕምሮ ህሙማን መርጃ ማህበር መስራች ሚኪያስ ለገሰ፤ ሁሉም ዜጋ ማእከሉን ከመጎብኘት ጀምሮ የቻለውን ሁሉ ድጋፍ እንዲያደርግ ጠይቀው በስዊዘርላንድ ድጋፍ በማሰባሰብ ለማህበሩ ላበረከቱት ግለሰብ ምስጋና አቅርበዋል።
ሰሊሆም የአእምሮ መረጃ ማህበር በ2008 ዓ.ም የተመሰረተ ሰብአዊ ተቋም ሲሆን ከ200 በላይ የአዕምሮ ህሙማንን አሁን ላይ እየረዳ መሆኑ ታውቋል።
